Tuesday, August 2, 2016

አበሻው ባንዴራ - ጎንደር ላይ ታየ!!

እነሆ! በቅፅል ስሙ "አምባሻው" ተብሎ የሚታወቀው "የኢትዮጵያ ባንዴራ" ባለፈው ሰንበት ማለትም ሃምሌ 31 2016 ቄሶችና ሼኮች በተገኙበት፣ መቶ ሺህ በሚገመት ህዝብ ሸኚነት የቀብር ስነስርአቱ በበጌምድር ጠቅላይ ግዛት ተፈመ ማለት ይቻል ይሆን? "ምነው ተኛ?" በሚል በሃሜት ድቅቅ አድርገን እንደ ክትፎ ስንከትፈው የሰነበትነው የአማራ ህዝብ ተደራጅቶና ተዘጋጅቶ፣ የቴዎድሮስን ከተማ ሲያንቀጠቅጣት ዋለ። 
መንጌ ቴክሱ እንዳለው፣ "በርግጥ አማራ አለ?" እያልን ስናጠያይቅ ሰንብተን ነበርና ክስተቱ አነቃቂ ለመሆን በቅቷል። በቅርብ ከማውቃቸው የOLF ጓደኞቼ ጋር ቡና እየጠጣን የጎንደሩን የተቃውሞ ሰልፍ በትኩረት ተከታተልነው። ከሁለቱም ብሄሮች ጋር ባንድ ጊዜ መጋጨት እንደማያዋጣው ያወቀው ወያኔ ጥይት ሳይተኩስ የተቃውሞ ሰልፉ ተጠናቀቀ። ሰልፈኞቹ የያዟቸው መፈክሮች አነጋጋሪ ነበሩ።

·        በኦሮሞ ወንድሞቻችን ላይ የሚካሄደው ግድያ ይቁም!
·        ስብሃት! ኢትዮጵያ አትፈርስም። በመቀበሪያችሁ ዋዜማ ላይ ናችሁ!!
·        ወልቃይት ብረሳሽ አጥንቴ ይርሳኝ! እስረኞች ይፈቱ!!
·        ወያኔ እንጂ ወልቃይት የሻእቢያ ተላላኪ አይደለም!!
·        የህወሃት የበላይነት ይቁም!
·        የታገልነው ትግሬ ለመሆን አይደለም!!
·        አማራ አሸባሪ አይደለም!!

          ባንዴራ የለበሱ ጦረኞች እና ጎራዴኞች በሰልፉ ላይ በብዛት ይታዩ ነበር። የጎንደር አማራ በሰልፉ ላይ በቁጣ ታየ። 25 አመታት በተለየ መልኩ የወያኔን ንቀት ተሸክሞ የኖረው ጎንደሬ "አሁንስ በቃኝ!" ሲል ተሰማ። "ተከዜን ትግሬ እንጂ ትግራይ ተሻግሮት አያውቅም" ሲል ቅኔውን መዠረጠው። "አማራ ፈሪ ነው" የሚለውን የነ ጄኔራል ሳሞራ የኑስ ሽሙጥ የሚያከሽፍ እምቢታ ታየ። የጎንደር ተቃውሞ ለወያኔ ራስ ምታት የሚሆነው ግን አምባሻው ባንዴራ ተወግዶ፤ ነባሩ የኢትዮጵያ ባንዴራ ጎንደር ከተማ ላይ ሲውለበለብ መዋሉ ነበር። ከፊሉን ጥያቄ ወያኔ አምኖ መቀበሉ መደናገጡን ይጠቁማል። ወያኔ አምኖ የተቀበለው "የህወሃት የበላይነት ይቁም!!" የሚለውን ሲሆን፣ ይህ ጥያቄ የብአዴን አባላት ነባር ጥያቄ ሆኖ የዘለቀ ነው። ከአመጹ ጀርባ የአንዳንድ የብኣዴን አመራር አባላት ትብብር ሊኖርበት እንደሚችል መጠርጠሩ አለምክንያት አይደለም።   

       ጎንደሬዎች ከጥንት ጀምሮ የሚታወቁባቸው ጥቂት ስንኞች አሉ።

      እንዲህ ጨሶ ጨሶ - የነደደ እንደሆን
      የአመዱ መጣያ  - ስርፋው ወዴት ይሆን?

     ወገራ አሳላፊ  - ደንቢያ እንጀራ ጣይ
     ተበላህ ጎንደሬ - አትነሳም ወይ?

     በትናንቱ የጎንደር አመፅ ደግሞ አዲስ ግጥም ተፈጥሮ አድሯል፣

     ከባልንጀራው  - ማታ የተለየ
     የአበሻው ሰንደቅ - ጎንደር ላይ ታየ

          የጎንደር የሰንበት ውሎ በኢሳት ቴሌቪዥን (ESAT) እና በሶሺያል ሜድያዎች ሲዘገብ ውሏል። ወያኔም ማታ በሁለት ሰአት ዜናው ሳይወድ ተገዶ ሰልፉን ከነቅሬታው በቴሌቪዠን አሳይቷል። "የጎንደር ህዝብ አምባሻውን ባንዴራ ትቶ፤ አበሻውን ባንዴራ ማውለብለቡ ህገመንግስቱን የጣሰ ነው" ሲሉም ተናገሩ። ለመሆኑ ህዝቡ አምባሻውን ባንዴራ ካልፈለገ ለምን ይገደዳል? ወያኔ ራሱም አንብቦት የማያውቀውን ህገመንግስት በተመቸው ጊዜ ብቻ እያገላበጠ ይጠቀምበታል። የOLFን ባንዴራ በመላ ኦሮሚያ ማውለብለብ ስጋት መሆኑ በቀረበት በዚህ ዘመን፤ ወያኔ "አረንጓዴ - ቢጫ - ቀይ ባንዴራ አታሳዩኝ" እያለ አለቃቀሰ። በሁለተኛው የአለም ጦርነት የህብረቱ ጦር ወደ በርሊን ሲገሰግስ ሂትለር ተቆጥቶ፣ "በርሊንን እንኳ አናስነካም" ስለማለቱ ይወሳል። ወያኔ በኦሮሚያ በዝረራ ተሸንፎ፣ አሁን ደግሞ ጎንደርን ለቆ ወደ ተከዜ ሲያፈገፍግ "ትግራይን እንኳ አናስነካም" የሚል መሰለ። ጊዜ ሲከዳ ብብት ይጋለጣል። በዘመነ ደርግ "ከተማ ሲያረጅ ደሴን ይመስላል" የሚል አባባል ነበር። ለሁለተኛ ጊዜ መንግስት ሲያረጅ ለማየት በቃሁ።

          ከዚህ በሁዋላ የወያኔ ስርአት ያበቃለት መሆኑን ለመተንበይ ፖለቲከኛ መሆን አያስፈልግም። የኦሮሚያ አመፅ በየአቅጣጫውና በየእለቱ ስለሚፈነዳዳ ዜና መሆኑ እንኳ እየቀረ ሄዷል። ወያኔ ከመዳከሙ ብዛት የአዲሳባን ቆሻሻ እንኳ የሚጥልበት ቦታ ተቸገረ። "ድንገት ትግራይ ሪፖብሊክ የሚቋቋም ከሆነ በአማራና በኤርትራ መካከሉ ላይ እንዳንጨፈለቅ የሱዳን ድንበር ያስፈልገናል" በሚል ከአማራ ክልል ቆርጠው የወሰዱት የወልቃይትና የሁመራ መሬትም ይኸው አደጋ ላይ ወደቀ።
          ስርአት ሲያረጅ ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ ከእጅ ይሾልካል።

          ጄኔራል ፃድቃን ገብረትንሳኤ ገብቶታል። የወያኔ ስርአት እንዳለቀለት አሳምሮ ገብቶታል። ስጋትም ሰንጎ ይዞታል። ማለትም ወያኔ ከወደቀ የሚመጣው መንግስት ስሙን ከወንጀለኞች ተርታ እንዳይፅፈው ሰግቷል። በቅርቡ የለቀቀውን መጣጥፍ የሚያነብ ይህንኑ በቀላሉ መረዳት ይችላል። መጪው መንግስት ጄኔራሉን ጠርቶ፣ "የራያ ቢራ ፋብሪካን የገነባኸው ገንዘቡን ከየት አምጥተህ ነው?" ብሎ እንዲጠይቀው አይፈልግም። "የደቡብ ሱዳን መንግስት የጦር መሳሪያ ሲገዛ ደላላ ሆኜ ያገኘሁት ገንዘብ ነው" ብሎ ለማሳመን ስለመቻሉ እርግጠኛ አይመስልም። ጄኔራል ፃድቃን ከግል ስጋቱ አንፃር ጭምር የህወሃትን ግማሽ አካል ከመሞት ለማዳን ቢነሳሳ አይደንቅም። የህወሃት ሰዎች ያለምንም ግርግር ስልጣናቸውን የሚያስረክቡ ከሆነ ግን የያዙትን ይዘው የግል ህይወታቸውን እንዲቀጥሉ መተው ይሻላል። ቂምን በቂም መመለስ አንድ ቦታ ላይ ካልተቋረጠ አዙሪቱ መቸም ቢሆን ማቋረጫ አይኖረውም።

          ትናንት ያገኘሁት የውስጥ መረጃ እንደሚጠቁመው በጎንደር አመፅ ምክንያት ማምሻውን የተወሰኑ የህወሃት ሰዎች አዲስአበባ ላይ ተሰብስበው ሲመክሩ ነበር። ነገሩ እንኳ ትልቅ ጉዳይ አይደለም። ብቻ በውይይቱ ላይ፣ "በሃይለማርያም በኩል በተዘዋዋሪ አገሩን መምራት አልተቻለም። ሃይለማርያም ተወግዶ አንድ ጠንካራ የኛ ሰው በቀጥታ አመራር ቢሰጥ ይሻላል።" የሚል አሳብ መነሳቱ ነው። ከጎንደር አመፅ ጋር በተያያዘ የብአዴን አመራር አባላት ከአርበኞች ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው እንደሚችል መጠርጠራቸውም ሌላው ነጥብ ነው።

በመጨረሻ "ቀጥሎ ምን ይሆናል?" የሚል ጥያቄ ይነሳል።

ጄኔራል ፃድቃን በቅርቡ ለንባብ ባበቃው ፅሁፉ ያቀረበው "ይሆናል" (Scenario) ሃሰት አዘል ስህተት ነው። ለአብነት "የኦሮሞ አመፅ መቆሙ" ሲል ይገልፃል። መቼ ቆመ? በመቀጠል ደግሞ፣ "የወያኔ ችግር ህገመንግስቱን አለማክበሩ ነው" ይላል። ለመሆኑ በአለም ላይ መጥፎ ህገ መንግሰት የፃፈ አለ እንዴ? እናወዳድር ቢባልስ ከወያኔ ያልተሻለ ህገመንግስት ማግኘት ይቻላል? የደርግ ህገመንግስትም እኮ የመናገርና የመፃፍ መብትን ይፈቅድ ነበር። አንድ መንግስት ከህገመንግስቱ አንድ ነጥብ እንኳ ከጣሰ ማድረግ ያለበት በሚቀጥለው ቀን ከስልጣን መውረድ ብቻ ነው። ጄኔራል ፃድቃን ግን ሃያ አመታት ሙሉ ህገመንግስቱን ሲጥስ የነበረው ስርአት እንደገና አዲስ የሽግግር ስርአት እንዲዘረጋ እድል እንዲሰጠው ይመክራል።

ዞረም ቀረ "ቀጥሎ ምን ይሆናል?" የሚል ጥያቄ ከፊታችን አለ።

በጎንደር የተጀመረው አመፅ ወደ ባህርዳር እና አዲስአበባ ሊስፋፋ የመቻል እድሉ ሰፊ ነው። የኦሮሚያ ወጣቶች በተለያየ ስልት አመፃቸውን ይቀጥላሉ። የአዲሳባ ቆሻሻ ወደ ኦሮሚያ እንዳይደፋ ከልክለዋል። የወያኔ አውቶብሶችን ከማቃጠል ድርጊቶች ባሻገር ሌላም አይነት እንቅፋቶች መፍጠሩ ሊቀጥል ይችላል። ምናልባት ቀጣዩ እርምጃ አዲስአበባ ከኦሮሚያ ውሃ እንዳታገኝ ቧንቧዎችን መቁረጥ ሊሆን ይችላል። እንዲህ በአመፅ እየተናጠ የሚሄደው ስርአት የመጨረሻ እድሉ አገሪቱን አዘረክርኮና ለህገወጥ ተግባራት አጋልጦ መውደቅ ነው።

ከመውደቁ በፊት ግን ወያኔ አንዳንድ ሙከራዎችን ማድረጉ አይቀርም።

ለአብነት ወያኔ በራሱ ላይ መፈንቅለ መንግስት ሊያካሂድ ይችላል። ጄኔራል ሳሞራ የኑስ ቤተመንግስት ሊገባ ይችላል። ፃድቃንም ተመሳሳይ ነገር ቢመኝ አያስደንቅም። መቸም ሳሞራና ፃድቃን አገር ለመምራት ከመንግስቱ ሃይለማርያም አያንሱም። መንግስቱ ምናልባት በአገር ፍቅር ስሜቱ ሊበልጣቸው ይችላል። "ቢወዳት ነው ቢጠላት አንቆ የገደላት?" እንዲሉ።

መሰንበቻውን የወያኔ የጎበዝ አለቆች ንብረት ወደ ትግራይ ሲያጓጉዙ እንደነበር ሲሰማ ቆይቷል። በተለይ ሰነዶች ላይ ትኩረት ማድረጋቸው ጥቆማ አለ። እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ የጦር መሳሪያዎች በአብዛኛው ትግራይ ናቸው። ለአብነት በመሃል አገር የተተኳሽ ማከማቻ መጋዘን የለም። ውቅሮ ተራራ ስር በተቀበረ ዋሻ ውስጥ ይገኛሉ። የደብረዘይት አየር ሃይል ቀፎውን ከቀረ አመታት አልፈውታል። ክምችቱ መቐለና አክሱም ነው። የህወሃት ደጋፊዎች የሰሯቸው ህንፃዎች በአብዛኛው በባንክ ብድር በመሆኑ ጥለው ለመሄድ አያሳስባቸውም ይሆናል። ቤተሰባቸውን ማሸሸት ከጀመሩም ሰነባብተዋል።

እንግዲህ የአዲሳባ ነገር የማያዋጣ ከሆነ የወያኔ ሰዎች ወደ መቀሌ አፈግፍገው የሚሆነውን ለማየት መሞከራቸው አይቀርም። በተለይም ወያኔ ሹልክ ብሎ ከአዲሳባ በመውጣት ኦሮሞና አማራ በቆንጨራ ሲጨራረስ ለማየት ሊመኝ ይችላል። ይህ እንዳይሆን በተለይ የፖለቲካው አክተሮች አስተዋይና ብልህ መሆን ይጠበቅባቸዋል። የመጀመሪያው ጥበብ ሌላው ወገን ልክ እንደራሱ ለአገሪቱና ለህዝቡ ፍቅር እንዳለው፤ ሃላፊነት እንደሚሰማው ማመን ነው። ጣሊያን ሲተርት፣ "በድሮ ትራክተር ያረሰ መለዋወጫ አያገኝም።" ይል ነበር።

Gadaa Ghebreab  -  የቅዳሜ ማስታወሻ  -  ttgebreab@gmail.com   -  August 3, 2016            

3 comments:

Tech with Estif said...

THANK YOU!!! "THE BLACK SOIL OF ADHA"

Anonymous said...

Abyot eyefeneda zimita yemeretik timeslaleh. Hzbu kante bzu ytebqal. Ye qdamie mastawesha ye chqunoch mastawesha new bahunu qewti seaat. Please hzbun aneqaqa lewedequt selamawi selfegnochm tnish neger belen.
Thanks

Anonymous said...

as always you are the great....your words are sharp as blade.